የኦሮሞ ነፃነት ግንባር ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ስብሰባ መግለጫ 

የኦሮሞ ነፃነት ግንባር ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ስብሰባ መግለጫ

መጋቢት 9, 2011 ዓ.ም

addaየኦሮሞ ነፃነት ግንባር ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ከመጋቢት 4 – 8, 2011 ዓ.ም ባደረገዉ ስብሰባ መነሻነት፣ በሀገሪቷ እና በኦሮሞ ህዝብ የነፃነት ትግል ህደት ላይ ሰፊ ዉይይት ካደረገ በኃላ ካለንበት ነባራዊ ሁኔታዎች አንፃር ለወደፊቱ የሚጠበቁብንን ተግባራትና አመለካከቶችን የሚንቃኝበት የሚከተሉትን ዉሳኔዎች በማስተላለፍ ስብሰባዉን ኣጠናቋል፡፡

  1. ባሁኑ ጊዜ የሚስተዋሉትን የፖለቲካ ችግሮች ከመፍታት አንፃር
    ለረጅም ዘመናት በኦነግ እና በኢትዮጵያ መንግሰት መካከል የነበረዉን አለመግባባት በጠረጴዛ ዙሪያ ዉይይት ለመፍታት ነሐሴ 01,2010 ዓ.ም ስምምነት መደረሱ የሚታወስ ነዉ፡፡ ሆኖም ይህ ስምምነት በሚፈለገዉ መጠን እና ፍጥነት ወደ ተግባር ሳይቀየር ቀርቷል ወይም ሂደቱ ተጓትቷል፡፡ ከዚህም የተነሳ ኦነግ የፖለቲካ ሥራዉን በነፃነት እንዳያከናዉን እክል ገጥሞታል፡፡ ከዚህም ጋር በተያያዘ ድርጅቱ ለፖለቲካ እና ህዝብ ማደራጃ ሥራ የከፈታቸዉ ቢሮዎቹ በተላያዩ ቦታዎች ተዘግቶበታል፣ የድርጅቱ አባላት እና ደጋፊዎች ታስረዋል እንድሁም ከስራ የማባረር እና ማስፈራራቶች በተለያዩ ቦታዎች መኖራቸዉ ስምምነቱን የሚቃረኑ ተግባራት ናቸዉ፡፡ ምንም እንኳን የኦሮሞ ነፃነት ሰራዊትን በተመለከተ በመግባባት እና በሰላማዊ መንገድ ለመጨረስ ስባል ለአባገዳዎች ተላልፎ የተሰጡ ቢሆንም የሰላማዊ ትግሉ ምህዳር በተለያዩ እንቅፋቶች የተሞላ ነዉ፡፡ ይህ ሆኖ ሳለ ኦነግ የሀገሪቱን ችግር በሰላማዊ መንገድ ለመፍታት እንዲሁም ነባራዊዉን ሁኔታ በትግስት እና በቆራጥነት ለመወጣት ብሎም ትግሉን ወደፊት ለመግፋት የገባዉን ቃል በድጋሚ ያድሳል፡፡ በኦነግ እና በኢትዮጵያ መንግስት መካከል ያለዉን ያለመግባባት በሰላማዊ ንግግር ይፈታ ዘንድ በኤሪትራ የተደረሰዉን ስምምነት ወደ ተግባር እንዲቀየር ኦነግ በሙሉ ልብ የሚሰራ መሆኑን በድጋሚ ያረጋግጣል፡፡ ከዚህም ጋር ተያይዞ በተለያዩ እስር ቤቶች ስቃይ እየደረሰባቸዉ ያሉትን የኦነግ አባላት እና ደጋፊዎች በአስቸኳይ እንዲፈቱ በተጨማሪም በኦሮሞ ህዝብና ሌሎችም ላይ የሰብዓዊ መብት ጥሰት እና የፖለቲካ መብቶች በደል ያደረሱ አካላትም በአስቸኳይ ለህግ እንድቀርቡ ኦነግ አጥብቆ ይጠይቃል፡፡
  1. ብሔር ብሔረሰቦች በትግላቸዉ ያገኙትን መብት ማስጠበቅን በተመለከተ
    ብሔር ብሔረሰቦች ለረዥም ዓመታት ባደረጉት መራራ ትግል የፌዴራል ስርዓትን በማዋቀር ብሔር ብሔረሰቦች ማንነታቸዉን የማስከበር እና እራስን በራስ የማስተዳደር መብት በመጠኑም ቢሆን አግኝቷል፡፡ ነገር ግን አንዳንድ ሀይሎች ይህንን የፌዴራል ስርዓት አፍርሶ በብሔር ብሔረሰቦች ፈቃድ ላይ ያልተመሰረተ፣ የማንነት እና ራስን በራስ የማስተዳደርን መብት ዕዉቅና የማይሰጥ የድሮ ስርዓትን በአንድነት ስም በሀይል መልሶ በህዝቦች ጫንቃ ላይ ለመጫን ሰፊ ዘመቻ ከፍቷል፡፡ የፌዴራል ስርዓቱን ለማፍረስ የሚደረገዉ መጠነ ሰፊ የሆነ አፍራሽ የፖለቲካ ዘመቻ ከፍተኛ እልቂት እና ዉጥንቅጥን ሊያስከትል የሚችል በመሆኑ ኦነግ ይህንን የፖለቲካ ሸፍጥ በጽኑ የሚቃወም ሲሆን፤ እንዲሁም የህዝቦች ሙሉ መብት ይከበር ዘንድ አጥብቆ ይታገላል፡፡ በተጨማሪም የፀረ ፌድራልዝሙ ዘመቻ እንዳይሳካ ኦነግ በተለየ ትኩረት ይሰራል፡፡
  1. ፊንፊኔን አስመልክቶ
    የኦሮሞ ህዝብ በፊንፊኔ ላይ ተፈጥሯዊ፣ ታሪካዊ እና ህጋዊ የባለቤትነት መብት አለዉ፡፡ በፊንፊኔ እና ኦሮሚያ መካከል የሚኖረዉ ድንበር ሳይሆን አስተዳደራዊ ወሰን ብቻ ነዉ፡፡ ፊንፊኔ የኦሮሚያ እምብርት እና ዋና ከተማ ናት፡፡ ሆኖም፣ ኦነግ በፊንፊኔ ነዋሪ የሆኑ የተለያዩ ብሔር ብሔረሰቦች እና ባዕዳን መብት በሕግ የተጠበቀ መሆኑን ከዚሁ ጋር ያረጋግጣል፡፡ ከዚህ ጉዳይ ጋር በተያያዘ ፊንፊኔን አመኃኝቶ ሌላ የፖለቲካ ፍጆታ ለማጋበስ ሲባል የጥላቻ እና አፍራሽ ፕሮፖጋንዳ የሚነዙት ወገኖች ከዚህ እኩይ ተግባራቸዉ በአስቸኳይ እንድታቀቡ ኦነግ ያሳስባል፡፡
  1. የኦሮሞ ፖለቲካ ድርጅቶች ህብረትን በተመለከተ
    የኦሮሞ ፖለቲካ ድርጅቶች ህብረት የኦሮሞ ህዝብ ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ማህበራዊ ጥያቄዎችን በመፍታት ረገድ ከፍተኛ አስተዋፆ ይኖረዋል፡፡ የኦሮሞ ፖለቲካ ድርጅቶች ህብረትን ዕዉን ማድረግ የሁሉም ኦሮሞ ህዝብ ፍላጎት እና ጥያቄም ነዉ፡፡ በኦሮሞ እና ኦሮሚያ ህልዉና ላይ የተጋረጠዉ አደጋ በሁላችን ህልዉና ለይ የተጋረጠ እንደመሆኑ መጠን፤ የኦሮሞን እና ኦሮሚያን ህልዉና ከጥፋት ለመታደግ የሁሉም የኦሮሞ ፖለቲካ ድርጅቶች ሃላፍነት መሆኑን ኦነግ ያምናል፡፡ ስለሆነም፣ የኦሮሞ ፖለቲካ ድርጅቶችን ህብረት በአስቸኳይ ዕዉን በማድረግ ህዝባችን በፍጥነት መብቱን እንዲጎናጸፍ ኦነግ ይህን ጉዳይ አስመልክቶ የምሠራ ኮሚቴ አዋቅሮ ወደ ሥራ አስገብቷል፡፡ የኦሮሞ ህዝብም ይህን ህብረት ዕዉን ይሆን ዘንድ የራሱን ድጋፍ እንድሁም አስፈላጊ ጫና እንድያሳድር ኦነግ አጥብቆ ይጠይቃል፡፡
  1. የተገኙ ፖለቲካዊ መብቶችን ማስጠበቅን በተመለከተ
    ብሔር ብሔረሰቦች ለጥያቄዎቻቸዉ ተገቢ መልስ መስጠት የሚችል አመራር እና መንግስትን ለማደራጀት ይችሉ ዘንድ የመደራጀት፣ ሐሳብን በነፃነት የመግለጽ፣ የመንቀሳቀስ፣ ቢሮ የመክፈት፣ የፈለጉትን ፓርቲ የመደገፍ እና ያልፈለጉትን የመቃወም መብቶች ሙሉ በሙሉ መከበር አለባቸው፡፡ እነዚህ መብቶች በህገመንግስቱ የተረጋገጡ ቢሆኑም በተለያዩ መንገዶች የፖለቲካ ምህዳሩ እየጠበበ መምጣቱ ተጨባጭ እዉነታ ነዉ፡፡ በመሆኑም መንግስት የፖለቲካዉን ምህዳር ለማስፋት የገባዉን ቃል እንዲያከብር ኦነግ በድጋሚ ያስታዉሳል፡፡ ሁሉም የሀገሪቱ ብሔር ብሔረሰቦች በከፈተኛ ትግል ያገኙትን መብቶች አጥብቆ በመያዝ የተጀመረዉን የሽግግር ለዉጥ እንዳይደናቀፍ ብሎም ወደኋላ እንዳይመለስ የራሳቸዉን ድርሻ እንዲያበረክቱ ኦነግ በጥብቅ ያሳስባል፡፡

ድል ለኦሮሞ ህዝብ !

የኦሮሞ ነፃነት ግንባር
መጋቢት 9, 2011 ዓ.ም