በወይዘሮ ብርሃኔ ማሞ ላይ የተፈጸመው ግድያ በሁሉም ሰብዓዊ ፍጡር ሊወገዝ ይገባል

በወይዘሮ ብርሃኔ ማሞ ላይ የተፈጸመው ግድያ በሁሉም ሰብዓዊ ፍጡር ሊወገዝ ይገባል

(የኦነግ መግለጫ – ሓምሌ 25 ቀን 2018ዓም)

addaሓምሌ 23 ቀን 2018ዓም ማታ በምዕራብ ኦሮሚያ የቄሌም ወለጋ ዞን ዋና ከተማ ከሆነችው ከደምቢ-ዶሎ ከተማ የተሰማው ለሰሚ ጆሮ የሚከብድ አሰቃቂና አሳዛኝ ዜና ነው። ለወሊድ ምጥ ላይ የነበርችዋ ኦሮሞ እንስት፡ ወ/ሮ ብርሃኔ ማሞ፡ ቤተሰቦቿ ለወሊድ ወደ ሆስፒታል ይዘዋት በመሯሯጥ ላይ ሳሉ በደምቢዶሎ ከተማ ቀበሌ 04 ውስጥ መንገድ ላይ የኢህኣዴግ መንግስት ያሰማራቸው ወታደሮች ባዘነቡባት የጥይት እሩምታ ምጡን ሳትገላገል በማህጸኗ ካለው ልጅ ጋር ተገደለች።

ይህንን በኢትዮጵያ መንግስት በወይዘሮ ብርሃኔ ማሞ ላይ የተፈጸመውን ማንኛውም ሰብዓዊ ፍጡር እንደሱ ባለ የሰው ልጅ ላይ ይፈጸማል ተብሎ የማይታሰበውን ኣረመኔያዊ ግድያ የኦሮሞ ነጻነት ግንባር በጥብቅ ያወግዛል። ሁሉም ሰላም-ወዳዶችም ይህንን የኢትዮጵያ መንግስት ወታደሮች በኣስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ በነበረች ነፍሰ-ጡር እንስት ላይ የፈጸሙትን አረመኔያዊ ግድያ አጥብቀው እንዲቃወሙ ኦነግ ጥሪውን ያቀርባል።

የኦሮሞ ነጻነት ግንባር በኦሮሚያና ከዚያም ውጪ ባሉ ኣካባቢዎች በተለያዩ ጊዜያት በኢትዮጵያ መንግስት የተፈጸሙትን ግድያዎች ሲያወግዝ ነበር። ከማውገዝ ኣልፎም የግድያ ወንጀሉን የፈጸሙት ለህግ ቀርበው እንዲጠየቁና በደባ የተገደሉ ዜጎች ፍትህ ይፋ እንዲሆን በተደጋጋሚ ሲጠይቅ መቆየቱ ይታወሳል። አሁንም ይህን በወ/ሮ ብርሃኔ ማሞ ላይ የተፈጸመውን አሰቃቂ ግድያና በኦሮሚያ የተለያዩ ኣካባቢዎችና ከኦሮሚያ ውጪም በሰላማዊ ዜጎች ላይ በኢትዮጵያ መንግስት በመፈጸም ላይ ያሉትን ግድያዎች በድጋሚ ኣጥብቀን እያወገዝን ሁሉም ወንጀለኞች ለህግ እንዲቀርቡ እንጠይቃለን።

የህዝብ ጥላቻ ያላቸውንና ሰብዓዊ ርህራሄ የሌላቸውን ሃይሎች ወደ ህዝቡ በማሰማራት ሰላማዊውን ህዝብ እንዲያውኩና ይህን መሰሉን አሰቃቂ ግድያ እንዲፈጽሙ እያደረገ ያለው የኢትዮጵያ መንግስት ከዚህ ጸረ-ህዝብ ድርጊቱ በአስቸኳይ እንዲቆጠብ ኦነግ አጥብቆ ይጠይቃል። ይህ መንግስት በማንኛውም መልኩ ወንጀል የፈጸሙትን ኣባላቱንና ኣካላቱን ለህግ ማቅረብና መሰል ወንጀል በቀጣይነት እንዳይፈጸምም ሃላፊነቱን እንዲወጣ አክሎ ያስገነዝባል።

ባጠቃላይ በኢትዮጵያ ኢምፓየር ውስጥ በተለይም በኦሮሚያ ውስጥት በተለየ ሁኔታ ደግሞ በደምቢዶሎና በዞኑ ውስጥ ያለው ሁኔታ እጅግ አስከፊ ወደ ሆነ ሁኔታ እያመራና አሳሳቢ እየሆነ ነው። ስለሆነም ሁሉም ሰላም-ወዳዶች፣ የተለያዩ አካላትና የኢትዮጵያ መንግስትም ይህንን ሁኔታ ለማስቆምም ሆነ በአካባቢው ዘላቂ ሰላም እንዲሰፍን ለማድረግ አብረን እንድንሰራ የኦሮሞ ነጻነት ግንባር ጉዳዩ ለሚመለከታቸው ሁሉ ጥሪውን ያቀርባል።

ዘመኑ የጭቆና ፍጻሜ ዘመን ነው !
ድል ለኦሮሞ ህዝብ !

የኦሮሞ ነጻነት ግንባር
ሓምሌ 25 ቀን 2018ዓም