ሰላም ይስፈን ዘንድ ጦርነቱ ቆሞ ስምምነታችን ልታደስና ልጠናከር ይገባል

ሰላም ይስፈን ዘንድ ጦርነቱ ቆሞ ስምምነታችን ልታደስና ልጠናከር ይገባል

(የኦነግ መግለጫ – ጥር 07, 2019 (ታህሳስ 29 2011ዓም)

addaኦነግ በመራዉ የኦሮሞ ሕዝብ የነጻነት ትግልና ሕዝባችን (በተለይም ቄሮ) በከፈለዉ ዉድ መስዋዕትነት ኢሕአዴግ ተገዶ ለሰላም ጥሪ መልስ እንድሰጥ በመደረጉ ላለፉት 8 ወራት ለሁሉም የሚጠቅም የሰላም መስኮት/ዕድል የተከፈተ ወይም የተፈጠረ መስሎ ነበር። የኦሮሞ ነጸነት ግንባርም መታደሱንና ለሰላም ዝግጁነቱን ከተናገረዉ የኢሕአዴግ መንግስት ጋር በሰላም አብሮ ለመስራት ከስምምነት ደርሶ፣ ሁሉንም ወገኖች በሰላማዊ መንገድ አብሮ ለመስራት በሚያስችል ስርዓት ዉስጥ የበኩሉን አስተዋጽዖ ለማበርከት ወሰነ። በዚህም የኢትዮጵያ መንግስትና ኦነግ በመካከላቸዉ የነበረዉን ጦርነት ለማቆም የጋራ ዉሳኔ ላይ ተደረሰ።

ይሁን እንጂ እስካሁን ኢሕአዴግና የመንግስት ስርዓቱ ከጸረ-ዴሞክራሲ ኣቋምና ኣካሄዱ ፈቀቅ ባለማለቱ እዉነተኛ መስዋዕትነት የከፈሉት ወገኖች ለዉጡን ለማሳካትና ስርዓቱንም ለማሻሻል ተሳታፊ እንድሆኑ ኣልተደረገም። በመሆኑም በስርዓቱ የሚካሄዱ ኣፈናዎች፣ እስራት፣ ግድያ፣ እና ሌሎችም የዴሞክራሲና የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ዛሬም ድረስ እንደቀጠሉ ናቸዉ። ለዚህም ማሳያ ልሆኑ ካሚችሉት በጥቂቱ:

  1. በተደጋጋሚ በኦሮሞ ሕዝብና በኦሮሞ ነጻነት ሠራዊት ላይ (በተለይ በምዕራብ ኦሮሚያ) በኢሕአዴግ ሠራዊት እየተካሄዱ ያሉ ጦርነቶች
  2. ከድንበር ጉዳይ ጋር ተያይዞ በሓረርጌ፣ በባሌ፣ በቦረና፣ በጉጂ፣ በወሎና በወለጋ በኩል በሰላማዊ (ትጥቅ-ኣልባ) ሕዝባችን ላይ እየተካሄዱ ያሉ ጦርነቶች
  3. በመላዉ ኦሮሚያ በሰፊዉ እየተካሄዱ ያሉ ኣፈና፣ እስራት፣ ግድያና የተለያዩ ኢ-ሰብዓዊና ኢ-ዴሞክራሲያዊ ድርጊቶች
  4. በተደጋጋሚና በስፋት (የመንግስት ከፍተኛ አመራር አባላት ሳይቀሩ እየተሳተፉበት) በኦነግና በኦሮሞ ነጻነት ትግል ላይ የሚካሄዱ የስም ማጥፋት ዘመቻና ፕሮፓጋንዳዎች
  5. በኦነግና በመንግስት መካከል የተደረሰዉ ስምምነት እንዳይተገበር ሆን ተብሎ የኦነግ ከፍተኛ ኣመራር ፍንፍኔ ከገባበት ዕለት ጀምሮ በርካታ የተለያዩ ዓይነት እንቅፋቶችን በመፍጠርና ኦነግ ጽ/ቤቶቹን ከፍቶ በኣግባቡ እንዳይንቀሳቀስና እንዳይሰራ ለማደናቀፍና ለመገደብ እየተሰሩ የቆዩና ያሉ ደባዎች

የኦሮሞ ሕዝብ ትግልና የኦነግ ጥላቻ የተጠናወታቸዉን ሓይሎችና ሚዲያዎችን በመታገዝ የሚካሄዱት እነዚህ ኣፍራሽ ድርጊቶች የኦሮሞን ሕዝብና የነጻነት ትግሉን ለከፍተኛ የአደጋ ስጋት ኣጋልጠዉት እንደሚገኙ በግልጽ ይታያል። ይህ ደግሞ ለሃገሪቷ ሰላምም በጎ ኣስተዋጽዖ ይኖረዋል ተብሎ ኣይታሰብም። ስለሆነም ይህን ችግር በጊዜና በኣግባቡ ለመፍታት፣ ብሎም ስምምነቱና ለዉጡ መንገዱን እንዳይስት ለማድረግ፥

  1. ሁሉም ሰላም ወዳድ ወገኖች፣ በተለይ ደግሞ የኦሮሞ ሕዝብ ይህ መንግስት እያካሄደ ያለዉን ጦርነት እንድያቆም ኣስፈላጊ ጫና ማድረግና
  2. በኦነግና በኢትዮጵያ መንግስት መካከል የተደረሰዉን ስምምነት (በተለይ ደግሞ የኦሮሞ ነጻነት ሠራዊትን የሚመለከት) ኣሁን የተፈጠረዉን ኣድስ ሁኔታ ለማስታረቅና ለመፍታት በሚያስችል ሁኔታ ለማሳደስና ለማጠናከር (to consolidate)፣ ሦስተኛ ወገን በሚገኝበት በአድስ እንድንወያይበት ጥሪ እናቀርባለን።

ኦነግ በበኩሉ በማንኛዉም ሁኔታ ዉስጥ በሰላማዊ መንገድ መሥራቱን እንደሚቀጥልበት በድጋሚ ያረጋግጣል።

ድል ለኦሮሞ ሕዝብ !

የኦሮሞ ነጻነት ግንባር
ጥር 07, 2019 /ታሕሳስ 29 2011 ዓም