በኦሮሚያ በወጣቶች ላይ ተነጣጥሮ እየተፈጸመ ያለው ግድያ የደህንነት ስጋት እየተባባሰ በመሄድ ላይ መሆኑን ያመልክታል

Obsi

በኦሮሚያ በወጣቶች ላይ ተነጣጥሮ እየተፈጸመ ያለው ግድያ የደህንነት ስጋት እየተባባሰ በመሄድ ላይ መሆኑን ያመልክታል

(የኦሮሞ ነጻነት ግንባር መግለጫ –ጥቅምት 25, 2020ዓም)

በመላው ኦሮሚያና በኣፍሪካ ቀንድ ቀጣና ላይ ባጠላው የደህንነት ቀውስ ህዝቡ በከፍተኛ ስጋት በተዋጠበትና እንደኦሮሞ ነጻነት ግንባር(ኦነግ) ያሉ ለህዝባቸው መብት የሚፋለሙ የፖለቲካ ድርጅቶች ለመፍትሄው ጥረት በማድረግ ላይ ባሉበት በዚህ ወቅት በወጣቶች ላይ ተነጣጥሮ እየተካሄደ ያለው ዘመቻ ችግሩ እየተባባሰ በመሄድ ላይ መሆኑን ያመላክታል።

ኦነግ የዛሬው የነጻነት ትግል ዋስትናና የነገው ኦሮሚያ ተስፋ በሆኑ የኦሮሞ ወጣቶች ላይ ያተኮረው ግድያ በማናቸውም ኣካል ይፈጸም የሃገሪቷን ህጎችና ህገ-መንግስቱን፣ የኣለምኣቀፍ ስምምነቶችንና ሰብዓዊ ክብርን የጣሰና ፈጽሞ ተቀባይነት የሌለው በመሆኑ በጥብቅ ያወግዛል።

ሰሞኑን በደቡብ-ምስራቅ ኦሮሚያ ባሌ-ሮቤ፣ በምስራቅ ኦሮሚያ ኣወዳይና መቻራ እንዲሁም በምዕራብ ኦሮሚያ ነቀምቴ ከተማና በመላው ኦሮሚያ በኦሮሞ ወጣቶች ላይ በጠራራ ጸሃይ እየተፈጸመ ያለው ዘግናኝ ግድያ የኦሮሚያ ሰላምና ደህንነት ያለበትን ኣስከፊ ደረጃ በግልጽ ያሳያል።

የመንግስት መዋቅር በነበሩ የተለያዩ ኣካላት እንደተፈጸመ የህዝቡ እምነት የሆነው- የኦሮሚያ ወጣቶችን ከጎዳና ላይ፣ ከመኖሪያ ቤታቸው ኣውጥቶና ከተለያዩ ቦታዎች ኣድኖ የመግደል ዘመቻ፥ ህዝቡ የደህንነት ዋስትና እንደሌለው የሚያመላክት ከመሆኑም ማሻገር የኦሮሞን ትግል ለማደናቀፍ ሲሰሩ በነበሩ ኣካላት ተቀነባብሮ በመካሄድ ላይ ያለ ዘመቻ ነው ብለን እናምናለን።

ስለሆነም ህዝባችንና ባጠቃላይ የኦሮሚያ ዜጎች ወጣቶችን ከምድረ-ገጽ ለማጥፋት ያለመውን ይህንን እኩይ ሴራ በጋራ በንቃት እንዲጠብቁ መልዕክታችንን እናስተላልፋለን።

መላው የደህንነት ሃይሎች ኣባላት የሆናችሁ ሁሉ ከዚሁ ህዝብ ኣብራክ ነው የወጣችሁት፣ ቤተሰቦቻችሁና ዘመዶቻችሁም የሚኖሩት ከዚሁ ህዝብ ጋር ነው። በመሆኑም ታማኝነታችሁ ከኣብራኩ ለወጣችሁት፣ ኣብራችሁት ለምትኖሩትና ደህንነቱን ለማስጠበቅም ቃል ለገባችሁት ህዝባችሁ መሆኑን ተገንዝባችሁ፥ መሰል ወንጀሎችን ከመፈጸም እንድትቆጠቡና ህዝቡንም ከወንጀለኞች እንድትጠብቁ ወገናዊ ጥሪያችንን ኣጥብቀን እናቀርብላችኋለን።

ለኦሮሚያ ዜጎች መብት የምትታገሉ የፖለቲካ ድርጅቶችና ታጋዮች፣ መንግስታዊ ያልሆኑና የግል ተቋማት፣ የሙያና የሲቪክ ማህበራት ባጠቃላይ ኦሮሚያ ዜጎች፥ ህዝባችንንና ሃገራችንን ከተነጣጠረበት ከባድ ኣደጋ ለመታደግ የኦሮሚያ ብሄራዊ የሽግግር መንግስት እንዲቋቋም ኦነግ ላቀረበው ጥሪ በጎ ምላሽ ሰጥታችሁ በማሳካት ግዴታችሁን እንድትወጡ በድጋሚ እናሳስባለን።

በመጨረሻም እየተፈረካከሰ ባለው የመንግስት መዋቅር ቡድን የተለያዩ ኣካላት በየቦታው በህዝብ ልጆች ላይ ተነጣጥሮ በመፈጸም ላይ የሚገኘው የግድያ ዘመቻ ህዝቡ ለፍትህ፣ ለዲሞክራሲ፣ ለሰብዓዊ መብት መከበርና ለነጻነቱ መረጋገጥ እያካሄደ ያለውን ትግል ኣንዳች እርምጃ ወደኋላ የማይመልስ መሆኑን እያሳሰብን፡ ይህን ወንጀል የሚፈጽሙትና የሚያስፈጽሙትም ከታሪክና ከህግ ተጠያቂነት የማያመልጡ መሆኑን ኦነግ ለሁሉም ለመግለጽ ይወዳል።

ህዝባችን ከመታደን፣ ከመታሰር፣ ለሰቆቃ ከመዳረግና በኣሰቃቁ ሁኔታ መገደልን ጨምሮ በብዙ መልክ ከሚካሄድበት ዘመቻ ነጻ ሊወጣ የሚችለው የኦሮሚያ ብሄራዊ የሽግግር መንግስትን ኣቋቁሞ የኔ ነው ብሎ እምነት የሚጥልበት መንግስት ሲመሰርት ብቻ መሆኑን እያሳሰብን። ለዚህም ትግሉን እያጠናከረ ከተለያየ ኣቅጣጫ ለተደቀነበት የጠላት ጥቃት ለራሱ ጠንካራ ጥበቃ እንዲያደርግ በዚሁ ኣጋጣሚ መልዕክታችንን እናስተላልፋለን።

በወጣቶች ላይ በማነጣጠር በመላው ኦሮሚያ ውስጥ ለሁለት ዓመታት ሲካሄድ የቆየው፡ በመካሄድም ላይ የሚገኘው ግድያ የደህንነት ስጋቱን ይበልጥ ወደ ከፋ ደረጃ እያሸጋገረው መሆኑን ህዝባችን ተረድቶ ለመፍትሄው እንዲንቀሳቀስ እናሳስባለን።

ድል ለሰፊው ህዝብ!
የኦሮሞ ነጻነት ግንባር
ጥቅምት 25, 2020ዓም